በሴፕቴምበር 6 ቀን 1776 ተመሠረተ… የካውንቲውን ታሪክ የሚዘክሩ የመታሰቢያ ዝግጅቶችና በዓላት ተካሄዱ

በሜሪላንድ ግዛት በሕዝብ ብዛት ቀዳሚ የሆነው ሞንትጎመሪ ካውንቲ 250ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን አስመልክቶ ከተለያዩ የመታሰቢያ ዝግጅቶች ጋር የአካባቢውን ታሪክ ወደ ኋላ መለስ ብሎ የሚያይበት ትርጉም ያለው ጊዜ እያሳለፈ ነው።

በሴፕቴምበር 6 ቀን 1776 የተመሠረተው ሞንትጎመሪ ካውንቲ፣ ጸጥተኛ ከነበረ የገጠር መንደር ተነስቶ በአሁኑ ወቅት ከ1 ሚሊዮን በላይ የሕዝብ ብዛት ወዳለውና የሜሪላንድ ግዛት ዋነኛ ማዕከል ወደ ሆነ ከተማነት አድጓል።

የሞንትጎመሪ ካውንቲ ሥራ አስፈፃሚ ማርክ ኤልሪች ባወጡት መግለጫ “250ኛ ዓመት ላይ መድረስ እጅግ ትርጉም ያለው ምዕራፍ ቢሆንም፣ ታሪካችንን በአግባቡ ለማክበር ያለፉ ስህተቶችንና ጨለማ ገጽታዎችን በግልጽ መጋፈጥና መነጋገር አለብን” በማለት የራስን ታሪክ የመመርመርን አስፈላጊነት አጽንኦት ሰጥተዋል።

ሞንትጎመሪ ካውንቲ በሴፕቴምበር ወር ሙሉ የካውንቲውን የምሥረታ ሂደት የመሩ ዋና ዋና ሰዎችን፣ ቦታዎችንና ታሪካዊ ክስተቶችን የሚያጎሉ የተለያዩ ዝግጅቶችን ያካሂዳል።

በሌላ በኩል፣ በ250ኛው ዓመት የምሥረታ ሳምንት የማኅበረሰቡ ባህላዊ የሠራተኞች ቀን (Labor Day) በዓልም አብሮ ተከብሯል። በኬንሲንግተን እና በጋይተርስበርግ የአካባቢ ድርጅቶች፣ የኪነጥበብ ቡድኖችና የመንግሥት ባለሥልጣናት የተሳተፉበት የሠራተኞች ቀን ሰልፍ ተካሂዷል።

በተጨማሪም የካውንቲው ባለሥልጣናት በመጪው ሴፕቴምበር 11 ቀን በሮክቪል ኮርትሃውስ ስኩዌር ፓርክ ውስጥ ‘የሴፕቴምበር 11 የሽብር ጥቃት 25ኛ ዓመት’ መታሰቢያ ሥነ-ሥርዓት ያዘጋጃሉ። በዚህ የመታሰቢያ ሥነ-ሥርዓት ላይ በወቅቱ ሕይወታቸውን ያጡትን 11 የሞንትጎመሪ ካውንቲ ነዋሪዎችን ጨምሮ ወደ 3,000 የሚጠጉ ተጎጂዎች እና የአደጋ ጊዜ ፈጣን ምላሽ ሰጪዎች ላደረጉት ክቡር መስዋዕትነት ክብር ይሰጣል።